Sunday, October 29, 2017

የ “ወልደአብ” መወገዝ ያስደሰተን የምንፍቅና መጽሐፍ ስለሆነ እንጅ ቅባቶችን ለማበሳጨት አይደለም!




፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠


የዘንድሮው ቅዱስ ሲኖዶስ እንደ መጀመሪያው የመክፈቻው ቀን ቢሆን ኖሮ ቤተክርስቲያንን በታሪክ የሚያስወቅሳት ጉዳይ እንደነበር የታወቀ ነው፡፡ እንደ አንድ ልብ መካሪ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ሆነው በመንፈስ ቅዱስ የሚመራውን የሐዋርያት ጉባዔ በተከፋፈለ ሃሳብ ሲሰነጣጥቁት እና አንድ ልብ አንድ ሃሳብ መሆን ሲሳናቸው ሁላችንም አዝነን ነበር፡፡
ሆኖም ግን ከሁለተኛው ቀን ጀምሮ የተከፋፈለው ሃሳብ ሁሉ ተዘጋ እና አንድ ሃሳብ ላይ መድረስ ተቻለ፡፡ በዚህም መሠረት ምንም እንኳ ብዙ የምንጠብቀው ነገር ቢኖርም የተወሰኑ ውሳኔዎች ግን በጣም ጥሩዎች እንደነበሩ አልዘነጋነውም፡፡ የማኅበረ ቅዱሳን የቴሌቪዥን ሥርጭት ያለእኛ ፈቃድ በፓትርያርኩ ተጽእኖ ብቻ አይዘጋም ተብሎ ተወስኗል፡፡ የበጋሻው ደሳለኝ መወገዝ የአባ መዓዛ ስልጣነ ክህነት መያዝ የዘማሪት ምርትነሽ በይቅርታ መመለስ የቅባት ኑፋቄ ያነገበው “ወልደ አብ” የተባለው መጽሐፍ መወገዝ በቅባት ካህን የተጠመቁ ምእመናን ወደ ተዋሕዶ ሃይማኖታችን ሲመለሱ መጠመቅ አለባቸው የሚሉት ፍሬያማ ውሳኔዎች ናቸው፡፡ የአቡነ ሙሴን ጉዳይ ግን አጀንዳ መሆኑም ወደ መንበራቸው እንዳይሄዱ መታገዳቸውም ከጅምሩም አልገባኝም፡፡ ያም ሆነ ይህ ግን ጥሩ ጥሩ ውሳኔዎች እንደተወሰኑ ግን መረዳት አለብን፡፡
የምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከትን በተመለከተ እንደአጀንዳ የተያዘውን ጉዳይ ወደ ኋላ በመተው የአቡነ ማርቆስ ጉዳይ እንዳይታይ በቅዱስ ፓትርያርኩ የተደረገው ትግል ግን ምቹነት የለውም ነበር፡፡ “ወልደ አብ” የተባለው የክህደት መጽሐፍ በዚሁ ሀገረ ስብከት ታትሞ ሲሰራጭ መጽሐፉ የክህደት ነው በሚል ለመጀመሪያ ጊዜ ጩኸቱ የመጣው ከምእመናን ዘንድ ነበር፡፡ ይህ መጽሐፍ ሙሉው ክህደት መሆኑን ተመልክተን ለመነሻ ያህል የሚሆኑትን ነጥቦች ዘርዝረን ገልጸን ፊርማ አሰባስበን ለጎዛምን ወረዳ ቤተክህነት እና ለሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ገቢ አድርገናል፡፡ እንዲያውም የጎዛምን ወረዳ ቤተክህነት ሥራ አስኪያጅ የሆኑት ሊቀ ብርሃናት ተስፋ ዳኘው በዚህ መጽሐፍ ዙሪያ ብዙ ነገር አውርተውናል፡፡ እርሳውም ጉንደወይን በነበሩበት ጊዜ ብዙ ሥራ እንደሠሩ በመግለጽ የመጽሐፉ አሳታሚ ገብረ መድኅን እንዳለውም እንደሞተ የነገሩን እርሳቸው ናቸው፡፡ እኔ ራሴ ከሁለት ጓደኞቼ ጋራ በመሆን ነበር ይህን ደብዳቤ ያደረስነው፡፡ እንዲያውም በጣም ሲያስቀኝ የሚኖረውን ጉዳይ ዛሬ ልንገራችሁማ፡፡ ከጓደኞቼ ጋራ ሦስት ሆነን ነው ከጎዛምን ወረዳ ቤተክህነት ቢሮ የሄድነው፡፡ ዓላማችን ይህ የክህደት መጽሐፍ አባ ዐሥራት ገዳም ይሰራጫል ስለተባለ ያ ስርጭት እንዲታገድ በሚል ነበር የሄድነው፡፡ ሆኖም ግን አባ አስራት ገዳም በደብረ ማርቆስ ወረዳ ቤተክህነት እንጅ እኔ በምመራው በጎዛምን ሥር አይደለም አሉን እና ሌሎችን ወሬዎች ማውራት ጀመርን፡፡ ይህን መጽሐፍ እኔም ተመልክቸዋለሁ በጣም ክህደት ነው አሉ፡፡ እንዲያውም የጌታን ልደት ከሁለት ወደ ሦስት ቀይረው እንደጻፉት መልካሙ በየነ የሚባል ፌስቡክ ላይ በደንብ አብራርቶ ጽፎታል እዚያ ላይ ብታዩ ትገረማላችሁ አሉን፡፡ ፌስቡክ የምትጠቀሙ ከሆነ መልካሙ በየነ የሚጽፋቸውን ተመልከቱማ በጣም እያብራራ ነው እየጻፈው ያለ አሉን፡፡ እኔም በውስጤ ስቄ ከጓደኞቸ ጋራ ዓይን ለዓይን ተጠቋቁመን ፈገግ አልን፡፡

ከዚህ በኋላ ያደረግነው ለሀገረ ስብከቱ ደብዳቤውን ገቢ ማድረግ ነበር፡፡ የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪጅ እኛን ለመቀበል ፈቃደኛ ስላልነበሩ አንድ ጓደኛየ ነው ለሦስት ልጆች ገንዘብ ከፍሎ ወስደው እንዲያስገቡት ያደረገው፡፡ ልጆችን ከውጭ ሆኖ ጠብቆ አስገብተው ሲመለሱ ምን አሏችሁ ሲላቸው ዝም ብለው ነው ፋይል ያደረጉት ይሉታል፡፡ በነገራችን ላይ ዛሬ ቢፈተሽ ፋይል የትም ቦታ ፋይል ሆኖ እንደማይገኝ ይታወቃል፡፡ አቡነ ማርቆስ ማንም ፊርማ አሰባስቦ አልጠየቀኝም ብለው በድፍረት ለመናገር ያበቃቸው ደብዳቤው ከፋይሉ ወጥቶ ተቀዳድ ስለተጣለ ነው፡፡ እኛ ግን ቀሪው በእጃችን ስላለ አልገባም ቢሉንም እግዚአብሔርን ካልፈሩ መብታቸው ነው፡፡ ለወረዳ ቤተክህነት ፊርማ አስገብተን ዝም ሲሉ ለሀገረ ስብከት አስገባን ሀገረ ስብከቱም ጉዳዩን ቸል ሲለው ለጠቅላይ ቤተክህነት ፊርማችንን አሰባስበን አስገባን፡፡ ይህን ሲሰሙ ሊቀ ሊቃውንት ሰሎሞን ዳዊት “ወልደ አብ” የሚባለውን መጽሐፍ አምጡልኝ ዓይቸ መልስ ልስጥበት አሉን፡፡ የሚገርማችሁ እኮ ገና ለመጀመሪያ ጊዜ ይህ መጽሐፍ የደረሳቸው ለእርሳቸው ነበር አሁን መጽሐፉን አምጡልን የሚሉን ለሁለተኛ ጊዜ ነው፡፡ ባለፈው ሰጥተንዎታል እኮ ግን ምንም መልስ አልመለሱም ዛሬ ጉዳዩን ለጠቅላይ ቤተክህነት ስናደርሰው መጽሐፍ ፍለጋ የገቡ እንዲህ አድርገናል ለማለት ነው እንጅ መልስ ሊሰጡበት እንዳልሆነ እናውቃለን ብለን መጽሐፉን ሳንሰጣቸው ቀረን፡፡ እንዲያውም የእኛን አቤቱታ ተቃውመው አዲስ አበባ ከሄዱት መካከል ቁጥር አንድ ሊቀ ሊቃውንት ሰሎሞን ሆነው አረፉት፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ የጠቅላይ ቤተክህነት ሥራ አስኪጅ አቡነ ዲዮስቆሮስ ወደ ሊቃውንት ጉባዔ ሊመሩት ነው ሲባል ብዙ ጊዜ ፈጀ ያም ሆኖ ግን እስካሁን ድረስ ለሊቃውንት ጉባዔ ያ የሰበሰብነው ፊርማ አልደረሰም በዚህ በጣም እናዝናለን፡፡ ከዚህ በኋላ ነው እንግዲህ ጉዳዩን እንደ አዲስ በማንሣት ብጹእ አቡነ ዘካርያስ መጽሐፉን አውግዘው ለአቡነ ማርቆስም ግልጽ ደብዳቤ ጽፈው መጽሐፉ እንዲመረመር ለቋሚ ሲኖዶስ አቤት ብለው ለሊቃውንት ጉባዔ ያደረሱት፡፡ በዚህም መሠረት የሊቃውንት ጉባዔ ጉዳዩን ዓይተው መጽሐፉን ገጽ በገጽ ቃል በቃል ተመልክተው ባለ አምስት ገጽ ውሳኔ ለቅዱስ ሲኖዶስ ያደረሱ፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስም የሊቃውንቱን ጉባዔ የውሳኔ ሃሳብ መነሻ አድርጎ ዓርብ ጥቅምት ፲፯ ከሰዓት በፊት በነበረው ጉባዔ መጽሐፉን አውግዞ ለይቶታል፡፡ ከዚሁ ጋር በተያያዘ የተነሡ ጉዳዮችም መላ ተበጅቶላቸዋል፡፡
·        መጽሐፉ ከሚሠራጭባቸው ቦታዎች ሁሉ እየተሰበሰበ እንዲቃጠል፡፡
·        መጽሐፉ በታተመበት አካባቢ ለካህናት እና ለምእመናን የእቅበተ እምነት ሥራ መሥራት ሥልጠናዎችን መስጠት፡፡
·        ወልድ ፍጡር ብሎ በሚያምን በቅባት ካህን የተጠመቀ ሰው የልጅነት ጥምቀት መጠመቅ እንዳለበት፡፡ ጥምቀቱም ዳግም አይባልም፡፡
·        ሀገረ ስብከቱ ላይ ትኩረት የሚያደርግ ቋሚ ኮሚቴ እንዲዋቀር፡፡
·        “ሚሥጢረ ሃይማኖት ወትንቢተ ዘዝክሪ ወጳውሊ”  የሚለው ሁለተኛው የኑፋቄ መጽሐፍም በሊቃውንቱ ጉባዔ እንዲመረመር የሚሉ ትእዛዛት አብረው ተላልፈዋል፡፡
ሆኖም ግን እነዚህን ሁሉ ሥራዎች ለመሥራት የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ከቦታው መነሣት እንዳለባቸው ደፍረው አልተናገሩም፡፡ ይህንን ውሳኔ ተከትሎ በፌስ ቡክ ላይ ቅባትን እናስተምራለን የሚሉ አንዳንድ ልጆች አሁንም ከድርጊታቸው ባለመታቀብ የቅዱስ ሲኖዶስን ውሳኔ ሲቃወሙ ታይተዋል፡፡ እነዚህን ልጆች ያስተማሩትን ትምህርት በወረቀት ላይ በማተም ሙሉ አድራሻቸውን በመያዝ ለቅዱስ ሲኖዶሱ እምነታቸውን እንዲገልጡ በማድረግ ካልተመለሱ እንዲወገዙ መደረግ አለበት፡፡ “ወልደ አብ” የተወገዘው እኛን ለማስደሰት ቅባቶችንም ለማበሳጨት ሳይሆን መጽሐፉ አርዮሳዊ ስለሆነ ነው፡፡ በነገራችን ላይ ከዚህ መጽሐፍ ክህደት ጋር ተዛማጅነት ያላቸው ብዙ መጻሕፍት አሉ አልተወገዙም ምክንያቱም በቤተክርስቲያናችን ስም ስላልታተሙ ነው፡፡ ይህ መጽሐፍ ግን በድፍረት ጥንታዊቷን ገዳም ነው አሳታሚ ብሎ በፊት ገጹ ላይ ያስቀመጣት፡፡ ከመጽሐፎቹ ጋር በተያያዘ “ሚሥጢረ ሃይማኖት ወትንቢተ ዘዝክሪ ወጳውሊ” የሚለው በቀጣይ እንደሚወገዝ ምንም ጥርጥር የለውም፡፡ አሁን ላይ እየፈለግነው ያለው “መሠረተ ሃይማኖት” የሚለው “ሀ” ብለው ኑፋቄ የጀመሩበትን መጽሐፍ ነው፡፡ ይህ መጽሐፍ ያላችሁ ወንድሞቼ እህቶቼ አድርሱን፡፡ በቤተክርስቲያናችን ስም ኑፋቄ አይተላለፍ ነው የምንለው እንጅ ሰው የፈለገውን ማመን ይችላል መብቱ ነው ያውም ከፈጣሪ የተቸረው፡፡ በእኛ ቤተክርስቲያን ውስጥ ግን የእኛ ያልሆነን ነገር ማስተማር አይቻልም ያስቀጣል፡፡

ነገ በሚውለው የቅዱስ ሲኖዶስ ስበሰባ የምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት ጉዳይ ዳግም እንደሚነሣ እና የምእመናንን እንባ የሚያብስ ውሳኔ እንደሚተላለፍ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ይርዳን!
፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠
✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍
© መልካሙ በየነ
ጥቅምት ፲፱ / ፳፻፲ ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍

No comments:

Post a Comment