Sunday, October 29, 2017

የምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት ጉዳይ በቸልታ ባይታይ!




፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠
አሁን ለአቡነ ሳዊሮስ ለቅዱስ ሲኖዶስ ጸሐፊ የጽሑፍ መልእክት እንድናደርስ በተጠራው የተማጽኖ ጥሪ ላይ ብዙ ሰው እየላከ እንደሆነ ነው የሚታወቀው አሁንም ይላክ፡፡ ከምሥራቅ ጎጃም እያላችሁ በእነዚህ ስልክ ቁጥሮች የተማጽኖ መልእክት አድርሱ፡፡
0911862433 ላይ እባካችሁ የምሥራቅ ጎጃምን ህዝብ አቤቱታ መላ ስጡት እንበላቸው፡፡ አቤቱታ ባቀረብን ጊዜ የምስል የድምጽ እና ሌሎች ማንኛውንም መረጃ ለአቡነ ሳዊሮስ በእጃቸው በፍላሽ አድርገን የሰጠን ሲሆን እስካሁን ግን ምንም ዓይነት መረጃ እንዳልቀረበ ነው የተነገረው፡፡
**************************************
የምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት አሁን ባለበት ሁኔታ አስተዳደራዊ ብቻ ሳይሆን ሃይማኖታዊ በደልም እየተፈጸመበት ነው የሚገኘውው፡ ይህንንም ጉዳይ ለሰባት ጊዜ በራሱ ወጭ አቤቱታውን ለቅዱስ ሲኖዶስ ሲያሰማ የነበረው ጨዋው የምሥራቅ ጎጃም ህዝብ የዘንድሮውን የጥቅምት ሲኖዶስ የድካሙ ማረፊያ እንደሚሆን ገምቶ ነበር ሆኖም ግን በፓትርያርኩ እምቢተኝነት የምሥራቅ ጎጃም ህዝብ አቤቱታ አጀንዳ መሆን የለበትም ብለው በፈጠሩት አምባጓሮ በአጀንዳነት ሳይያዝ ቀርቷል፡፡ በትናትናው የቅዱስ ሲኖዶስ ውሎ ምሥራቅ ጎጃምን ብቻ ሳይሆን ዓለምን በሙሉ ሲያውቅ የነበረው የቅባቶች መጽሐፍ “ወልደ አብ” ተምርምሮ ውግዘት ተላልፎበታል፡፡ አሁን እየተሠራጨ ካለበት አካባቢም ተሰብስቦ እንዲቃጠል በተለይም መጽሐፉ ታትሞ በተሠራጨበት ጎንቻ ሲሶ እነሴ ወረዳ ቤተክህነት የእቅበተ እምነት ሥራ በሰፊው መሠራት እንዳለበት ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔውን አስተላልፏል፡፡ ይህንንም ተከትሎ መጽሐፉ የሚሠራጭባቸው ቦታዎች ምስካበ ቅዱሳን ቆጋ ኪዳነ ምሕረት አንድነት ገዳም ጎንቻ ሲሶ ውስጥ የሚገኝ እና አባ ዐስራት ገዳም ደብረ ማርቆስ ውስጥ የሚገኝ መጽሐፉን በመደበቅ ላይ እንደሆኑ ተነግሯል፡፡

በዚህ የክህደት መጽሐፍ ዙሪያ የተጠየቁት የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ አቡነ ማርቆስ “ወልደ አብ” የኑፋቄ መጽሐፍ መሆኑን አላውቅም ነበር በማለት በጉባዔው ሲሳለቁ ተስተውለዋል፡፡ እንዲያውም የዚህን የመጽሐፉን ጉዳይ በመሸፋፈን ነገሩን ወደ ማኅበረ ቅዱሳን ለማላከክ ሲሞክሩ ተስተውለዋል፡፡ “ማኅበረ ቅዱሳን ዳግም እያጠመቀ ነው” በማለትም ሲከሱ ውለዋል፡፡ ሆኖም ግን ብጹአን ሊቃነ ጳጳሳት በተለይም እነ አቡነ እንድርያስ፣ አቡነ ኤልሳዕ፣ አቡነ ሉቃስ፣ አቡነ ዘካርያስ፣ አቡነ አብርሃም፣ አቡነ ቀውስጦስ እና ሌሎችም ጉዳዩን በጥልቀት ስለሚያውቁት “ጥምቀት የሚያጠምቅ ቄስ እንጅ ማኅበረ ቅዱሳን አይደለም፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ሥራው ማስተማር ብቻ ነው” ብለው መልሰውላቸዋል፡፡ አቡነ ማርቆስም ብጹአን ሊቃነ ጳጳሳትን በመሳደብ ለማሸማቀቅ ሞክረዋል፡፡ በዚህም የተነሣ ጥቅምት ፲፯ ከሰዓት በኋላ በተደረገው ስብሰባ የአቡነ ማርቆስ የዲሲፕሊን ጉዳይ ታይቶ ይቅርታ እንዲጠይቁ ተደርጓል፡፡ ብጹአን አባቶች እንዳሉት “ከጳውሎስ ሳምሳጢ የተጠመቀ ሰው ቢኖር ይጠመቅ” ይላልና በቅብአተ መንፈስ ቅዱስ ከበረ ባዮች ወደ ርትእት ተዋሕዶ እምነታችን ሲመለሱ መጠመቅ እንደሚገባቸው አሳስበዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከትን የሚከታተል ቋሚ ኮሚቴ ተዋቅሯል፡፡ በምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት ዙሪያ ያስተዳድሩታል ይመሩታል ብለን እምነት ልንጥልብዎ አንችልም ተብለው አቡነ ማርቆስም ተገስጸዋል ተመክረዋል፡፡

ከፍተኛ ፍጥጫ የነበረበት የትናንትናው የቀትር በኋላው ስብሰባ አቡነ ማርቆስ ላይ ከፍተኛ ወቀሳ ደርሶባቸዋል፡፡ “የክህደት መጽሐፍ ታትሞ ሲሰራጭ አላውቅም የሚሉ ምን እየሠሩ ነው” ተብለው ከምልአተ ጉባዔው ደረቅ ጥያቄ የተተየቁት ብጹእነታቸው ምልአተ ጉባዔውን በማሸማቀቅ ለማለፍ ጥረት አድርገዋል፡፡ አቡነ እንድርያስ እና አቡነ ቀውስጦስ ከፍተኛ ክርክር ያደረጉ ሲሆን አቡነ አብርሃም እና አቡነ ዘካርያስም በከፍተኛ ቁጭት ለምእመናን በመጨነቅ በአቡነ ማርቆስ ላይ ወቀሳቸውን ሰንዝረዋል፡፡ አቡነ ሳዊሮስም በጣም በማዘን “መንፈስ ቅዱስ የሚመራውን ጉባዔ እንዲህ እላፊ ቃል መነጋገሪያ ሲሆን ማየት በጣም ያሳዝናል” ብለዋል ተብሏል፡፡
የምሥራቅ ጎጃም ህዝብ በጉጉት የሚጠብቀው ጉዳይ የአቡነ ማርቆስን ከሀገረ ስብከቱ መነሣታቸውን ጉዳይ ነው፡፡ አቡነ ማትያስ እና አቡነ ማርቆስ ግን የተስማሙበት ነገር ያለ ይመስላል፡፡ ምልዓተ ጉባዔው ከምሥራቅ ጎጃም እንዲነሡ ውሳኔ እንዳያስተልልፍ ይቅርታ ይጠይቁ ብለው የመከሯቸውም ይመስላል፡፡ የዕቅበተ እምነቱ ሥራ የሚራው አቡነ ማርቆስ ሀገረ ስብከቱ ላይ እያሉ ከሆነ በጣም ትልቅ ፈተና ነው፡፡ “ሚሥጢረ ሃይማኖት ወትንቢተ ዘዝክሪ ወጳውሊ” የሚለው ሁለተኛው የክህደት መጽሐፍም በሊቃውንት ጉባዔ እንዲታይ ምልአተ ጉባዔው ወስኗል፡፡ ነገር ግን እነዚህን የምልዓተ ጉባዔውን ውሳኔዎች ተግባራዊ ለማድረግ አቡነ ማርቆስ መነሣት የለባቸውም ነበር ወይ? የሚለው ጉዳይ ይታሰብበት ባይ ነኝ፡፡ ምእመናንን በማያውቁት ነገር ለምን እናስጨንቃቸዋለን ለምንስ እንፈታተናቸዋን፡፡ #ብጹአን_ሊቃነ_ጳጳሳት_ሆይ! የምሥራቅ ጎጃምን ሀገረ ስብከት እንዲህ በቀላሉ ባታልፉት መልካም ነው፡፡ “ወልድ ፍጡር ነው” የሚለውን ትምህርት በመድረክ እያስተማሩ ያለበትን ሁኔታ ማስቆም ይኖርብናል ይኖርባችኋል፡፡ በቀላሉ በስልጠና ይፈታል ተብሎ የሚታለፍ ጉዳይ አይደለም፡፡ ነገሩ የተወሳሰበ እየሆነ ነው ያለው፡፡ ይህንን ትምህርት አሰልጥነው በተለያዩ ቦታዎች እንዲስተምሩ የተዋቀሩ ማህበራትም እንዳሉ መረጃው አለን፡፡ ስለዚህ የማያዳግም ምላሽ ለመስጠት ይመች ዘንድ የአቡነ ማርቆስ ጉዳይ ይታሰብበት፡፡

በአቡነ ማርቆስ ላይ የቀረበ ምንም ዓይነት ክስ የለም መረጃችሁ ተደብቆ ነው የቀረው ያሉን የመረጃ ምንጮች አሁንም በቀጥታ መረጃውን ለብጹአን ሊቃነ ጳጳሳት ማድረስ እንደሚገባ ተነግሯል፡፡ ስለዚህ አዲስ አበባ አካባቢ የምትገኙ ልጆች ይህን የምስል እና የድምጽ መረጃ በተለይ ለብጹእ አቡነ ዘካርያስ እንዲደርስ ይደረግ፡፡ አቡነ ዘካርያስ ይህንን መረጃ ለምልአተ ጉባዔው በማቅረብ አቡነ ማርቆስ እንዲነሡ ከፍተኛ ጥረት እያደረጉ ናቸው ተብሏል፡፡
አሁን ለአቡነ ሳዊሮስ ለቅዱስ ሲኖዶስ ጸሐፊ የጽሑፍ መልእክት እንድናደርስ በተጠራው የተማጽኖ ጥሪ ላይ ብዙ ሰው እየላከ እንደሆነ ነው የሚታወቀው አሁንም ይላክ፡፡ ከምሥራቅ ጎጃም እያላችሁ በእነዚህ ስልክ ቁጥሮች የተማጽኖ መልእክት አድርሱ፡፡
0911862433 ላይ እባካችሁ የምሥራቅ ጎጃምን ህዝብ አቤቱታ መላ ስጡት እንበላቸው፡፡

፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠፠
✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍
© መልካሙ በየነ
ጥቅምት ፲፰ / ፳፻፲ ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ
✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍✝✍

No comments:

Post a Comment