Sunday, March 26, 2017

የቅብዓት ምንፍቅና ምንጭ---ክፍል ፰


© መልካሙ በየነ
መጋቢት 18/ 2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ

ምንም እንኳ ሁሉም የቤተክርስቲያናችን መጻሕፍት “ወልድ ዋሕድ በተዋሕዶ ከበረ” በሚለው ትምህርት ላይ የተባበሩ መሆናቸው የታወቀ ቢሆንም ለማስረጃነት ያህል የተወሰኑ ጥቂት ትምህርቶችን እናስቀምጥ፡፡ ወልድ ራሱን እንዳከበረ የሚናገሩ ትምህርቶች፡፡
1.  “ዘአንገሦ ለሥጋ አዳም በመንፈስ ቅዱስ ወረሰዮ ቅዱሰ ወማሕየዌ፤ በመንፈስ ቅዱስ ሕይወትነት የአዳምን ባህርይ ያከበረዉ የባሕርይ አምላክ ያደረገዉ እርሱ ነው” ሃይማተ አበው ዘአልመስጦአግአያ  ም 2 ቁ 5
2.  ሃይማኖተ አበው ዘቄርሎስ ላይ እንዲህ ተጽፎ እናገኘዋለን፡፡ ስምዐት 124÷34 “ወካዕበ ይቤ እስመ ክርስቶስ ኢተቀብዐ በእንተ መፍቅድ ዘቦቱ አላ ለሊሁ ቀባዒ ውእቱ ወዐርገ ኀበ ሥልጣነ መለኮቱ እንዘ ሰብእ ውእቱ ወለሊሁ እግዚአብሔር አምላክ ተብህለ በእንቲአሁ ከመ ውእቱ ተለዐለ ፈድፋደ በእንተ ትህትና ወሕጸጽ እንተ ዘትስብእት ወንዴት ወለሊሁ ጸገዎ ስመ ዘላዕለ ኩሉ ዝንቱ ዘኮነ በህላዌ ከመ አምላክ ከመ ያልዕለነ ለነሂ ዓዲ ኀበ ሀሎ ዝኩ፤ ዳግመኛ ክርስቶስስ ክብር መሻት ኖሮበት አልከበረም እርሱ ራሱ አክባሪ ነው እንጅ ሰው ቢኾንም በባህርይ ክብሩ ከበረ እርሱ ራሱ እግዚአብሔር አምላክ ነው ሥጋ ትሁት ሕጹጽ ነዳይ ስለሆነ ተለዐለ ተብሎ ተነገረለት ከሁሉ በላይ የሆነ ስምንም እሱ ራሱ ሰጠው ተባለ ይህም የሆነ በባህርይ ተዋሕዶ ነው አምላክ እንደሆነ እኛንም እሱ ወደ አለበት ያቀርበን ዘንድ”
3.  “ወከመዝ ነአምሮ ለሊሁ ተቀብዐ ከመ ሥርዓተ ትስብእት ወዳእሙ ውእቱ ዘይቀብዕ ርእሶ በመንፈሱ ባሕቲቱ፤ በተዋሕዶ እንደከበረ እናውቃለን ግን በገዛ ሥልጣኑ ራሱን የሚያከብር እሱ ነው”  ሃይማኖተ አበው ስምዓት ምእራፍ 124 ክፍል 2 ቁጥር 14 ላይ፡፡
4.  “መኑ ውእቱ ዝንቱ ዘሐደሶ ለሥጋ እምነ ኀጉል ወተወክፎ እሙስና፤ ሥጋን ከብልየቱ ያደሰው ከመለወጥ አድኖ የተዋሐደው ይህ ማነው” የሚለውን ጥያቄ ማን ነው ብለህ ትመልሳለህ? እልመስጦአግያ ም 4 ቁ 11
5.  “አነ እቄድስ ርእስየ፤ እኔ ራሴን አከብራለሁ” ዮሐ 17÷19
6.       በቃል ክብር መክበር ለሥጋ ተገባዉ፡፡ርሳነ ቄርሎስ 76÷ 1
7.       ከአብ የተገኘ ቃል ከተዋሐዳት ካከበራት ከሥጋ ጋር አንድ እንደሆነ መጠን.ቄር.56÷15
8.        ሰዉ መሆንን ከወደደ ሰዉ አለመሆንን ከጠላ ሰዉ መሆንን ስለወደደ ከአብ በሚገኝ ክብር ከበረ ተባለ ከአብ የተገኘ ክብርም አካለ ቃል ነዉ ክብርነቱ ለተዋሐደዉ ሥጋ ነዉ፡፡ርሳነ ቄርሎስ 56÷3-4
9.  በመንፈስ ቀዱስ አዋሐጅነት ከአብ በተገኘ ክብር ከብሯልና ከአብ የተገኘ ክብርም አካለ ቃል ነውከሌላ ክብር አይሻም ቃልን ከበረ የሚል አንቀጽ የለምና መሢህ የሚለዉ ክብር ነዉ ክብር ማለትም ከተዋሕዶ በፊት ክብር ያልነበረዉ ሥጋ አንድ አካል አንድ ባሕርይ በመሆን ከቃል ጋር ሲዋሐድ የባህርይ ክብርን በተዋሕዶ ገንዘብ ማድረጉን መናገር ነዉርሳነ ቄርሎስ  47÷9-10፡፡
10.  “ይህ ክብር በጸጋ በኅድረት እንዳልተሰጠው በዚህ ይታወቃል፤ በአንድ የመለኮት ባሕርይ ተዋሕዶ ነው አንጅ ለወልድ የአባቱ ልዑል ጌትነት ገንዘቡ ነውና” ሃይማኖተ አበው ዘባስልዮስ ም 33 ቁ 29
11.  “ዳግመኛ በዚህ ድርሳን እግዚአብሔር ሊዋሐደው ሥጋን እንደ ፈጠረ ተናገረ የመላእክት ፈጣሪ ሥጋ ያልነበረው እውነተኛ ፀሐይ ከንጹሕ ሥጋ ተወለደ ነቅፎ አልተወውም ንፁህ አድርጎ ፈጥሮ ፍጹም አምላክ አደረገው እንጅ” ሃይማኖተ አበው ዘዮሐንስ አፈወርቅ ም 68 ክ 29 ቁ 44
12.  “በሥጋ ከመጀመሪያው ሰው ከአዳም ከአብርሃም ከዳዊት ከተገኘ ባህርይዋም ኃጢአት የሌለበት በነፍስ በሥጋ ፍጹም የሚሆን አካልን ሊዋሐደው ፈጠረ ከማርያም የነሣውን ሥጋ ከኃጢአት ከዘር የራቀ አደረገው ከማኅጸን ጀምሮ በማይመረመር ግብር በአንድ ባሕርየ መለኮት ከእርሱ ጋር አንድ አደረገው” ሃይማኖተ አበው ዘቄርሎስ ም 70 ቁ 20
ከላይ የተዘረዘሩትን ጥቂት ማስረጃዎች እንደምሳሌ ካነሣን “ወልድ ራሱን የሚያከብር አምላክ ነው” ብለን “በተዋሕዶተ መለኮት ሥጋ ክቡር አምላክ ሆኗል” እንላለን፡፡ ለማንኛውም ግን ሃይማኖተ አበውን ሁላችሁ እንድታነብቡ እመክራችኋለሁ፡፡ ይህን ረቂቅ የተዋሕዶ ምሥጢር በጎላ እና በተረዳ በምሳሌ አስደግፈው አባቶቻችን ሊቃውንቱ በዚያ ጽፈውታል፡፡ ስለዚህ ይህን በዚህ ልፈጽመውና ወደ ሌላኛው ነጥብ እንለፍ፡፡
ይቆየን፡፡
ይቀጥላል፡፡

No comments:

Post a Comment