Monday, March 13, 2017

ዓለም አቀፍ የቤተክርስቲያን ጉባኤያት---ክፍል ፬




© መልካሙ በየነ

መጋቢት 5/ 2009 ዓ.ም
ደብረ ማርቆስ፣ ኢትዮጵያ

የጉባኤው መደምደሚያ ቃለ ግዘት
የኒቅያውን ጉባኤ ከፈጸሙ እና ከላይ የገለጽናቸውን ድርሳናት ካዘጋጁ በኋላ ላለፈውም ለሚመጣውም የኑፋቄ ትምህርት ቃለ ግዘታቸውን አስቀምጠዋል፡፡ እነዚህ ሃይማኖታቸው የጸና ምግባራቸውየቀና ሠለስቱ ምዕት ከዚህ ጉባኤ በኋላ “ከዚህ ኦርቶዶክሳዊ የሃይማኖት ቀኖና አልፈው አንዱን አካል ወልድን ከአብ ለይተው ያልነበረበት ጊዜ ነበረ የሚሉ ወይም ከመወለዱ በፊት አልነበረም የሚሉ ከኢምንት ወይም እምኀበ አልቦ ተፈጠረ የሚሉ ወይም ወልደ እግዚአብሔር ከአብ የተለየ ከሌላ ከባእድ ባሕርይ የተገኘ ነው የሚሉ ወይም ፍጡር ነው የሚሉ ወይም በባሕርይው መለወጥ አለበት የሚሉትን እነዚህን ሁሉ በሁሉ ያለች ዓለም አቀፋዊትና ሐዋርያዊት ቤተክርስቲያን ታወግዛቸዋለች” በማለት ቃለግዘታቸውን አስተላልፈዋል፡፡  
አርዮስ ከጉባኤ ኒቅያ በኋላ
አርዮስ በኒቅያው ጉባኤ ከተወገዘ በኋላም ከክህደቱ አልተመለሰም፡፡ ሠለስቱ ምዕት ይህንን ጉባኤ አርዮስን እና ግብረአበሮቹን በማውገዝ ከለዩአቸው በኋላ የአርዮስ ክህደት ለሁሉ ተጋልጦ ነበርናንጉሥ ቆስጠንጢኖስ አርዮስን እና ግብረአበሮቹን አጋዛቸው፡፡ ሠለስቱ ምዕት ትምህርታቸውን ሲያወግዝ ንጉሡ ደግሞ ግዞትን ፈረደባቸው፡፡ ከዚህ ግዞት በኋላ ትንሽ እንደቆዩ የተመለሱ የተጸጸቱ መስለው ኒቅያ የተሰበሰቡትን አባቶቻችን ውሳኔ ተቀብለናል ማለት ጀመሩ፡፡ ንጉሡም በተለያዩ ተጽእኖዎች ከግዞት እንዲመለሱ አድረጓል፡፡ ከዚያም በኋላ አርዮስም እንደሌሎቹ ሁሉ አምኛለሁ ተመልሻለሁ ብሎ ስለነበር ከግዞት አብሮ ተመልሷል፡፡ እለእስክንድሮስ ግን በአርዮስ መመለስ ደስተኛ አልነበረም በዚህም የተነሣ የአርዮስ ግብረ አበር የነበረው አውሳብዮስ አንተ የማትቀበለው ከሆነ አርዮስን የሚቀበል ፓትርያርክ በቦታህ እንተካለን እያለ ያስፈራራውና ያስጠነቅቀው ነበር፡፡ በዚህም የተነሣ እለእስክንድሮስ እንዲህ ያለ አሳዛኝ ፈተና በቤተክርስቲያን ላይ  ከምታመጣብኝስ እኔን ወይም አርዮስን ውሰደን ብሎ ወደ ፈጣሪው በመሪር እንባ ጸለየ፡፡ ከዚህ በኋላ አርዮስ ቀረበና ካመንክማ ንስሐ ገብተህ ሥጋ ወደሙን ስትቀበል እንይህ ተባለ፡፡ ከዚያም እሽ ምን አግዶኝ ሥጋውን በልቼ ደሙንም ጠጥቼ አሳያችኋለሁ ብሎ ቀነ ቀጠሮ ተያዘ፡፡ ከዚያም የተቀጠረው ቀን ደርሶ ከቤተክርስቲያንገብቶ ቅዳሴው ሲጀመር “አሃዱ አብ ቅዱስ አሃዱ ወልድ ቅዱስ አሃዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ” ሲሉ ሰማ፡፡ እርሱም በልቡ “ፍጡሩን ከፈጣሪ ጋር አንድ ያደርጉታልን” ብሎ አሰበ፡፡ በዚህን ጊዜ ሆዱ ታወከ ቅዳሴውን አቋርጦ ሊጸዳዳ ወደ መጸዳጃ ቤት ሄደ፡፡ ከዚያ እንደገባም ውስጥ ዕቃው በሙሉ ተዘርግፎ ተቀስፎ ሞቷል፡፡ የአርዮስ ፍጻሜው በእንዲህ ያለ መቅሰፍት ሆኗል፡፡
============================================================
፪.ጉባኤ ቁስጥንጥንያ
ቁስጥንጥንያ በታናሿ እስያ ክፍል የምትገኝ ቦታ ናት፡፡ ይህ ጉባኤ ሠልስቱ ምዕት አርዮስን እንዳወገዙበት እንደጉባኤ ኒቅያ ሁሉ በቤተክርስቲያናችን ተቀባይነት ያለው ጉባኤ ነው፡፡ ይህ ጉባኤ የኒቅያ ጉባኤ ከተደረገ ከ56 ዓመት በኋላ በ381 ዓ.ም በ150 ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን  የተደረገ ነው፡፡ ወልድ ፍጡር የሚሉ አርዮሳውያን በጉባኤ ኒቅያ ተወግዘው ከቤተክርስቲያን አንድነት ከተለዩ ከብዙ ዓመታት በኋላ ከእነርሱ ወገን የሆነ አንድ መቅዶንዮስ የተባለ መናፍቅ “መንፈስ ቅዱስ ህጹጽ ነው” ብሎ ክህደቱን ጀመረ፡፡ ይህ የመቅዶንዮስ ምንፍቅና ከቁስጥንጥንያው ንጉሥ ከቴዎዶስዮስ ቀዳማዊ ዘንድ እንደደረሰ ንጉሡ ይህ የቤተ ክርስቲያን ችግር በጉባኤ እንዲፈታ መልእክት አስተላለፈ፡፡ በዚህም የንጉሡ መልእክት መሠረት 150 ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ለአውግዞተ መቅዶንዮስ ተሰበሰቡ፡፡ ይህን ጉባኤ በመጀመሪያ ጎርጎርዮስ ዘእንዚናዙ ከዚያም ኔክታሪዎስ ወደመጨረሻም የእስክንድርያው ጢሞቴዎስ በሊቀመንበርነት መርተውታል፡፡
፪.፩ በጉባኤቁስጥንጥንያ የተነሡ መሰረታዊ ነጥቦች
በዚህጉባኤ የተሳተፉ 150 ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ለመሰብሰባቸው ምክንያት የመቅዶንዮስ የክህደት ትምህርት ቢሆንም ሌሎችን ጉዳዮችንም ተመልክተዋል፡፡ በመሠረታዊነት የተመለከቷቸው ነጥቦች የሚከተሉት ናቸው፡-
v  መንፈስ ቅዱስ ሕጹጽ ነው የሚለውን የመቅዶንዮስ የክህደት ትምህርት ማውገዝና መቅዶንዮስንም ከቤተክርስቲያን አንድነት መለየት፣
v  ቃለ እግዚአብሔር በተዋሕዶ ከድንግል ማርያም በተወለደ ጊዜ ከድንግል ማርያም የነሣው ሥጋን ብቻ ነው እንጅ ነፍስን አልነሳም በማለት ያስተምር የነበረውን መናፍቅ አቡሊናርዮስን እና ይህን ክህደቱን አውግዘው መለየት፣
v  እግዚአብሔር ወልድ የተዋሐደው ሥጋ በቅድምና የነበረን ሥጋ ነው እንጅ የአዳምን ሥጋ አይደለም የሚሉ መናፍቃንን ማውገዝ እና መለየት፣
v  በኒቅያ ጉባኤ ላይ ሠለስቱ ምእት ባዘጋጁት ጸሎተ ሃይማኖት ላይ ተጨማሪ የሃይማኖት ቀኖናዎችን መጨመር፣
እነዚህን መሠረታዊ ጉዳዮች በመንፈስ ቅዱስ መሪነት በአግባቡ ተመልክተው ውሳኔዎችን በመስጠት ድርሳናትን በመጻፍ አጠናቅቀዋል፡፡
ይቆየን፡፡
ይቀጥላል፡፡

No comments:

Post a Comment