Tuesday, August 5, 2014

ምሥጢረ ሥላሴ

ምሥጢረ ሥላሴ የሚለው ቃል ከሁለት ቃላት ማለትም “ምሥጢር” እና “ሥላሴ” ከሚሉት የተሰናሰለ ሲሆን ምሥጢር ማለት ስውር፣ ሽሽግ፣ ድብቅ፣ ሕቡእ ማለት ነው፡፡ ሥላሴ ማለት ደግሞ “ሠለሰ” ሦስት አደረገ ካለው የግዕዝ ግስ የወጣ ሲሆን ትርጉሙም “ሦስትነት” ማለት ነው፡፡ “ምሥጢረ ሥላሴ” ማለትም ፍጡራን የማይመረምሩት የሁሉ አስገኝ እግዚአብሔር ማንም በማይመረምረው ጥበቡ “ሦስት ሲሆን አንድ፤ አንድ ሲሆንም ሦስት” የመሆኑ ነገር የሚነገርበት ከ5ቱ አእማደ ምሥጢራት አንዱ ነው፡፡
“ሥላሴ” እንደ እናት እና እንደ ምድር ሁሉን ቻይ ናቸውና በሴት አንቀጽ “ቅድስት ሥላሴ” እንላለን ይኸም ማለት ልዩ ሦስትነት ማለት ነው፡፡ ልዩ ሦስት የሚያሰኛቸው “አንድ ሲሆኑ ሦስት፤ ሦስት ሲሆኑም” አንድ መሆናቸው ነው፡፡ አንድነታቸውም በመፍጠር፣ በመግደል፣ በህልውና፣ በአሳብ፣ በፈቃድ፣ በሥልጣን፣ በምልዐት፣ በስፋት፣ በቅድምና፣ ዓለምን በማሳለፍ፣ በመለኮት፣ በአገዛዝ፣ በባሕርይ እና በመሳሰለው ሲሆን ሦስትነታቸውም በስም፣ በአካል፣ በግብር ነው፡፡
- የስም ሦስትነት፡- አብ፣ ወልድ፣ መንፈስ ቅዱስ ይባላሉ፡፡ በአብ ሥም ወልድ ወይም መንፈስ ቅዱስ አይጠሩበትም፤ በወልድ ስምም አብ ወይም መንፈስ ቅዱስ አይጠሩበትም፤ በመንፈስ ቅዱስ ስምም አብ ወይም ወልድ አይጠሩበትም፡፡
- የአካል ሦስትነት፡- አብ ፍጹም ገጽ፣ ፍጹም አካል አለው፤ ወልድም ፍጹም ገጽ፣ ፍጹም አካል አለው፤ መንፈስ ቅዱስም እንዲሁ ፍጹም ገጽ፣ ፍጹም አካል አለው፡፡
- የግብር ሦስትነት፡- የአብ ግብሩ ወልድን መውለድ፣ መንፈስ ቅዱስን ማስረጽ ሲሆን የወልድ ግብሩ ደግሞ ከአብ መወለድ ነው፡፡ የመንፈስ ቅዱስ ግብሩ ከአብ መስረጽ ነው፡፡ አብ ወላዲ አስራጺ ይባላል እንጅ ተወላዲ ወይም ሰራጺ አይባልም፤ ወልድም ተወላዲ ቢባል እንጅ ወላዲ ወይም ሰራጺ ወይም አስራጺ አይባልም፤ መንፈስ ቅዱስም ሰራጺ ቢባል እንጅ አስራጺ፣ ወላዲ ወይም ተወላዲ አይባልም፡፡
ሥላሴ ማለት ልዩ ሦስትነት ማለት ነው ስንል እንደ ቀዳሜ ፍጥረት አዳም አንድ አንልም ሦስት ነውና እንደ አብርሃም፣ ይስሐቅና ያዕቆብም ሦስት የምንል አይደለም አንድ ነው እንጅ፡፡ አዳም አንድ ቢሆን ሦስት መሆን አይችልም፡፡ አብርሃም፣ ይስሐቅና ያዕቆብም ሦስት ቢባሉ የባሕርይ አንድነት የላቸውም፡፡ ስለዚህም ከዚህ ሁሉ በተለየ መልኩ “ሦስት ሲሆን አንድ፤ አንድ ሲሆን ሦስት” በሥላሴ ባሕርይ ያለ ልዩ ሦስትነት ነው፡፡ ይህንንም እኛ በምንረዳው መጠን ሊቃውንት የተለያዩ ምሳሌዎችን ያቀርባሉ፡፡
 ፀሐይ፡- ፀሐይ ክበብ፣ ሙቀት፣ ብርሃን አሏት፡፡ ነገር ግን አንድ ፀሐይ ብትባል እንጅ ሦስት ፀሐዮች እንደማንል ሁሉ በግብር፣ በስም፣ በአካል ሦስት የሆነ እግዚአብሔር አንድ አምላክ ቢባል እንጅ ሶስት አማልክት አይባልም፡፡
 እሳት፡- እሳት ሙቀት፣ ብርሃን ፣ አካል አለው፡፡ ነገር ግን አንድ እሳት ይባላል እንጅ ሦስት እሳት እንደማይባል ሁሉ በግብር፣ በስም፣ በአካል ሦስት የሆነ እግዚአብሔር አንድ አምላክ ቢባል እንጅ ሶስት አማልክት አይባልም፡፡
 ውኃ፡- ውኃ እርጥበት፣ ግዝፈት፣ እርቀት አለው፡፡ ነገር ግን አንድ ውኃ ቢባል እንጅ ሦስት ውኃዎች እንደማይባል ሁሉ በግብር፣ በስም፣ በአካል ሦስት የሆነ እግዚአብሔር አንድ አምላክ ቢባል እንጅ ሶስት አማልክት አይባልም፡፡
 ነፍስ፡- ነፍስ ለባዊት፣ ነባቢት. ሕያዊት ናት፡፡ ነገር ግን አንድ ነፍስ እንጅ ሦስት ነፍሳት እንደማንል ሁሉ በግብር፣ በስም፣ በአካል ሦስት የሆነ እግዚአብሔር አንድ አምላክ ቢባል እንጅ ሶስት አማልክት አይባልም፡፡
በእርግጥ እነዚህ የተሰጡት ምሳሌዎች እኛ እንድንገነዘበው ያህል እንጅ የሥላሴን ምሥጢር በትክክል የሚያረዱ ሁነው አይደለም፡፡
የእግዚአብሔርን አንድነት የሚያስረዱ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ማስረጃዎች
ዘፍ1፡1፣ ዘዳ6፡4፣ መዝ17፡31፣ ኢሳ43፡ 1-3፣ ሮሜ 1፡13፣ ዮሐ10፤30፣ ኤፌ 4፡6፣ ያዕ2፡19 ወ.ዘ.ተ
የእግዚአብሔርን  ሦስትነት የሚያስረዱ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ማስረጃዎች
ዘፍ1፡26፣ ዘፍ 18፡1-16፣ ኢሳ 48፡12-16፣ መዝ117፡17፣ ማቴ3፡16-18፣ ሉቃ1፡35፣ ዮሐ14፡15-17፣ ሐዋ20፡28፣2ኛቆሮ13፡14፣ ሮሜ8፡11፣ቲቶ1፡11፣ራዕ14፡1 ወ.ዘ.ተ
ሌሎችንም በርካታ ማስረጃዎች ስላሉ መጽሐፍ ቅዱስን መመልከት ይቻላል፡፡
VISIT:melkamubeyene.blogspot.com

No comments:

Post a Comment