Thursday, February 14, 2019

ወንጌል ቅዱስ ክፍል 9


=====================
 ሰባተኛ ጉባኤ

ወሳብዕ አርእስተ ነገር
ሰባተኛውን ክፍለ ነገር ብለውታል ክፍለ ነገር ይባላል ወአርእስተ ነገረ ዝንቱ መጽሐፍ ክቡር ክቡር የሚሆን የዚህ መጽሐፍ የነገሩ ክፍል 
እስመ ይእቲ ብይንት  የተለየች ናትና
ወውስቴታ ብያኔ ክሥት ፤  
በሷም የጎላ የተረዳ መለየት አለና ስለዚህ ነው በቃል በነገር ፤ ወበገቢር በሥራ ሁለት አርእስት ተናገረ ። ለሁለቱም ያመጣል ፤
በቃልስ እስመ ይእቲ ትነግር በእንተ ልደቱ ለእግዚአነ ወመድኃኒነ እምእግዝእትነ ማርያም ድንግል ንጽሕት ወአንሶስዎቱ ውስተ ዓለም ።
በቃል ያልሁት ንጽሕት ንዕድት ክብርት ከምትሆን ከመቤታችን መወለዱን በዚህ ዓለም ሠላሳ ሦስት ዓመት ከአራት ወር ከዐሥር ቀን መኖሩን ትናገራለችና ስለዚህ ነው። 
ወትኤዝዝ ኀበ ምግባራት ንጹሐት ወመሥመርያት ንጹሕት መሥመርያት የሚሆኑ ምግባራትን ታዛለችና ስለዚህ ነው፤
ወታሌቡ ዓዲ በጥይቅና ተስፋ በውሂበ ሕይወት ዘለዓለም ዘድልው እምነ ሠናያት ደኃርያት፡፡
ዳግመኛ በኋላ ዘመን ከሚገኝ ከበጐ ነገር ወገን ተዘጋጅቶ ያለውን የማያልፈውን ድኅነት በመስጠት የተስፋውን መረዳት ታስረዳዋለችና ስለዚህ ነው።
ወታዜክር ፈሪሃ ኩነኔ ወበቀል ዘበጽድቅ
በእውነት የሚደረግ ፈሪሃ ኩነኔን ፈሪሃ በቀልን ታሳስባለችና ስለዚህ ነው፤   
በአምጣነ ምግባራተ ሃይማኖት በሚሠሩት ሥራ መጠን  
ወአንሶስዎት ውስተ ዓለም ኃላፈ።  
ልብስን አንጽቶ ሠናፊልን አንሰርቶ አምሞ ጠምጥሞ መንደር ለመንደር በመዞር መጠን
ወፈቂድ ኀበ ነገር እኩይ 
ክፉ ነገርን በመውደድ ታዜክር አንድም ክፉ  ነገርን በመውደድ መጠን፤  
ጉዳት ያለበትን ነገር በመውደድ መጠን፡፡
ወቃላተ ጉሕሉት      
ክዳት ተንኮል ያለበትን ነገር በመውደድ መጠን
ታዜክር፡፡
እስከ ተፍጻሜተ ዝንቱ፤    
ሳብዕ አርእስተ ነገር ያለው እስኪፈጸም፡፡
ወኀበ ማኅለቅቱ፤  መላው እስኪፈጸም፡፡
ወበገቢርሰ እስመ ለለ፩ዱ እምሰባክያን ክፈለ ምዕራፈ ዚአሁ እምዕራፈ ካልኡ፡፡
ቃል ላለው ጨርሶ ገቢር ላለው አመጣ ፤ በገቢር ያልሁት ከአራቱ ወንጌላውያን አንዱም አንዱ እያለ አንዱም አንዱ ከባልንጀራው ምዕራፍ የራሱን ለይቷልና፡፡   
እምነ ፍኖት ነዊህ ወኀጺር፤
ረጅሙን ከረጅም አጭሩን ካጭር ፤ አንድም ረጅሙን ካጭር አጭሩን ከረጅም ።
ዘእንበለ ኃይለ ቃል ፤
ዝንቱ ውእቱ ወልድየ ካለው በቀር በዚህ አይለያዩም፡፡
ወተአምራት በረከተ ኅብስትን፤
ወስምዓት ጾራ፤
ወትእዛዛት  አንሰ እብለክሙ፡፡
ወምሳሌያት ምሳሌ ዘርዕ ከነዚህ በቀር፡፡
ወፈቃደ ኩሎሙ ዘበውስቴታ ፩ እሙንቱ ፤
በሱዋ ያለ የሁሉ ፈቃድ አንድ ነው ። አንድም ፈቂድ ዘበውስቴታ በሱዋ ያለውን በመሻት ሁሉ አንድ ናቸው።  
ኁልቈ አርእስተ ነገራት ዘ፬ቱ ወንጌላት ሰባክያን
በዘናመጽእ በከፊለ ምዕራፋተ ኃይለ ቃል 
የአራቱን ወንጌል የዓቢይ ምዕራፍ ቀጥር የነገሩን ምስጢር ምዕራፍ በመክፈል ጊዜ በምናመጣው አለ ። አንድም ከፍለን ከፍለን በምናመጣው አለ ።
ወኩሉ ነገር እምኔሆን ውስተ ቀዳሚሃ
ዓቢይ ምዕራፍ በመጀመሪያው ነው ያውም በሚመጣው ነው፡፡ ንኡስ ምዕራፍ ቀጥሎ በሚመጣው ነው ለሁለቱ ሁሉ፡፡
ብያኔ ሮማዊ ፪፻፲ወ፱ አርእስት
ሮማዊ ቁጥር ሮማዊ አቈጣጠር ሁለት መቶ ዐሥራ ዘጠኝ አርእስት ነው፡፡
ማቴዎስ ፷ወ፰ አርእስት  
ማቴዎስ ስሳ ስምንት አርእስት ነው 
ማርቆስ ፵ወ፰ አርእስት ፤
ማርቆስ አርባ ስምንት አርእስት ነው  ስሳና አርባ መቶ፣ ስምንትና ስምንት ዐሥራ ስድስት ነው፤ ነው፡፡ ዐሥራ ስድስትን ይዘህ ሂድ፡፡
ሉቃስ ፹ወ፫ አርእስት ።  
ሉቃስ ስማንያ ሦስት አርእስት ነው፤ አሥራ ስድስትና ሦስት ዐሥራ ዘጠኝ ።
ዮሐንስ ፳ አርእስት።    ዮሐንስ ሃያ አርእስት ነው ። ሃያን ከሰማንያ ላይ ብትደርበው መቶ ይሆናል ። ሁለት መቶ ዐሥራ ዘጠኝ ያለው ይህ ነው።   
ኁልቈ አርእስት ንኡሳን እንተ ተሠርዓ አቅማር እንበይነ ዚአሃ ዘአንበርዋ አበው ቅዱሳን አሞንዮስ ወአውሳብዮስ በረከተ ጸሎቶሙ የሃሉ ምበሌነ ለዓለመ ዓለም አሜን ።
ልመናቸው ክብራቸው ይደርብንና አበው ቅዱሳን ሐዋርያት የተናገሯት አሞንዮስ አውሳብዮስ የጻፏት ስለሷ ሰንጠረዥ የተጻፈላት፡፡ አንድም አበው ቅዱሳን አሞንዮስ አውሳብዮሰ አድርግ፡፡ አበው ቅዱሳን አሞንዮስ አውሳብዮስ የጻፏት ስለሷ የጻፉላት ሰንጠረዥ የተጻፈላት የንኡስ ምዕራፍ ቁጥር ፲፻ ወ፩፻ ፷ ወ፭ አርእስት  ሺህ መቶ ስሳ አምስት ነው፡፡
ማቴዎስ ፫፻ ፶ወ፭ አርእስት ፤
ማቴዎስ ሦስት መቶ አምሳ አምስት ነው ። አምስት ባለው ስድሰት ይላል ከውስጥ አግብቶ ሲዘራው፡፡ አምሰት ያለ እንደሆነ አንድ ወገን አድርጎ ስድስት ያለ አንደሆነ የመጨረሻውን ምዕራፍ ከሁለት ከፍሎ ነው ።  
ማርቆስ ፪፻ ፴ ወ፮ አርአስት 
ማርቆስ ሁለት መቶ ሠላሳ ስድስት አርእስት ነው ሦስት መቶና ሁለት መቶ አምስት መቶ ፤ አምሳና ሠላሳ ሰማንያ አምስትና ስድስት ዐሥራ አንድ።
ሉቃስ ፫፻ ፵ ወ፪ አርእስት ፤
ሉቃስ ሦሰት መቶ አርባ ሁለት አርአሰት ነው ።
አምስት መቶና ሦስት መቶ ስምንት መቶ ከአርባው ዐሥሩን ነሥተህ ከዘጠና ላይ ስትደርበው መቶ ይሆናል ። ዘጠኝ መቶ ሠላሳ ሦስት በል፡፡ 
ዮሐንስ ፪፻ ፴ ወ፪ አርእስት።
የዮሐንሰ ሁለት መቶ ሠላሳ ሁለት አርእስት ነው ፤
ሽህ ከመቶ ይሏል፡፡ ሠላሳና ሠላሳው ስሳ ነው  ሁለትና ሦስት አምስት ነው መላው ሽህ ሦስት መቶ ስሳ አምስት ነው ።
ወኁልቈ ምዕራፋት ዓበይት በመጽሐፈ ቅብጥ ፤
የዓቢይ ምዕራፍ ቁጥር በቅብጥ አቈጣጠር። ሐተታ ቋንቋው ቅብጥ ነውና በመጽሐፈ ቅብጥ አለ ፤ አንድም የገ የጸ ጸያፍ አለባቸውና ግብጽ ሲሉ ቅብጥ ይላሉ ፤ በግብጻውያን አቈጻጸር። 
፪፻ ፹ ወ፮ ምዕራፍ ።
ሁለት መቶ ሰማንያ ስድሰት ምዕራፍ ነው ።
ማቴዎስ ፻ ወ ፩ ምዕራፍ፤   
ማቴዎስ መቶ አንድ ምዕራፍ ነው
ማርቆስ ፶ ወ ፬ ምዕራፍቶ 
ማርቆስ አምሳ አራት ምዕራፍ ነው።
ሉቃስ ፹ ወ ፮ ምዕራፍ፤  
ሉቃስ ሰማንያ ስድስት ምዕራፍ ነው።
ዮሐንስ ፵ ወ ፭ ምዕራፍ
ዮሐንስ አርባ አምስት ምዕራፍ ነው ፤ ሐተታ አንድና አራት አምስት አምስትና አምስት ዐሥር አርባና አምሳ ዘጠና ፤ ዐሥርን ከዘጠና ብትደርበው መቶ ይሆናል ። ሉቃስ እንዳለው ። ሁለት መቶ ሰማንያ ስድስት ያለው ይህ ነው።
ወሶበ እንከ ዘከርነ በአምጣንነ ዘበጽሐት ኀቤሁ ክሂል እምአሕጽሮ ውስተ መጽሐፍ እስትጉቡዕ ፯ቱ እንተ አቅደምናሃ ቀዲሙ ንትሉኬ ኪያሃ በከመ ሠርዑ አበው አሞንዮስ ወአውሳብዮስ እምአቅማራት በተሰጠችን አእምሯችን በደረሰችበት መጠን አስቀድመን በተናገርነው በሰባቱ ክፍል የተሰበሰበውን በማሳጠር አሳጥረን ከተናገርን በኋላ፡፡ ኪያሃ ቀመረ፡፡ አሞንዮስ አውሳብዮስ እንደጻፉ አሥሩን ሰንጠረዥ እንጻፍ ።
በዚህ መጽሐፍ ግን ንኡስ ምዕራፍ ፬፻ ፲፩ ነው ። ማለት ማቴዎስ ፻፳፮፤ ማርቆስ ፹፮ ሉቃስ ፻፴፭። ዮሐንስ ፷፬፤ ዓቢይ ምዕራፍ ደግሞ ፹፱ ነው ። ማለት ማቴዎስ ፳፰፤ ማርቆስ ፲፮። ሉቃስ ፳፬ ዮሐንስ ፳፩ ነው።
በአንተ አኅብሮ ዘአርባዕቱ ወንጌላት ቅዱሳት
የአራቱ ወንጌላውያንን ነገር ለማስተባበር ።
ወረሰይዋ በማኅለቅት፡፡
ሳብዕ አርእስተ ነገር ያለው ሲፈጸም አደረጓት ።
በመትልወ ኅብረተ ቃሎሙ ።
የዘራቸውን አንድነት ቀጽሎ ቀጽሎ በመጻፍ አደረጉት፤ ሐተታ በመጀመሪያው አራቱ የተባበሩበትን በሁለተኛው ሦስቱ በሦስተኛው ሦስቱ የተባበሩበትን ፲ቱ አቅማር ተጠየቀት ጥቀ።  
ዐሥሩ ሰንጠረዥ ታወቀ ተረዳ።
ወላቲ ፮፻ ፶ወ፭ መስመር
ለሷም ስድስት መቶ አምሳ አምስት መስመር አሏት፡፡ ሐተታ ንዑስ ምዕራፍ በዛ መስመር አነሰሳ ቢሉ፡፡ ንኡስ ምዕራፍ እንደ ሰው እንደ እህል መስመር እንደ ቤት እንደ ውድማ ነው ፤ ባንድ ቤት ብዙ ሰው ባንድ ውድማ ብዙ እህል እንዲኖር ። ባንድ መስመርም ብዙ የንኡስ ምዕራፍ አኃዝ ይጻፋልና አምስት ባለው በዘጠነኛው ስንጠረዥ ዐሥራ ዘጠኝ ይላል፡፡ ይህን ዘጠኝ ያለ እንደሆነ ዘጠነኛውን ሀያ ይላል።
ቀመር ቀዳማዊ ማቴዎስ ወማርቆስ ሉቃስ ወዮሐንስ ፸ወ፪ መስመር።
አራቱ የተባበሩበት መጀመረያው ሰንጠረዥ ሰባ ሁለት መሰመር ነው እንዲህ እያልህ ሂድ።  ቀመር ዳግማዊ ማቴዎስ ወማርቆስ ሉቃስ ፻፲ወ፪ መስመር።
ሦስቱ የተባበሩበት ለሁለተኛው ሰንጠረዥ መቶ ዐሥራ ሁለት መስመር ነው ፤ መቶ ሰማንያ አራት ይሆናል።
ቀመር ሣልስ ማቴዎስ ወሉቃስ ወዮሐንስ ፳ወ፩ መስመር ።
ሦስቱ የተባበሩበት ሦስተኛው ሰንጠረዥ ሃያ አንድ መስመር ነው፡፡ ሃያውን ከሰማንያ ላይ ስትደርበው መቶ ይሆናል ፤ አራትና አንድ አምስት ሁለት መቶ አምስት ።  
ቀመር ራብዕ ማቴዎስ ወማርቆስ ወዮሐንስ ፳ወ ፮ መስመር ።
አራተኛው ሰንጠረዥ ሦስቱ የተባበሩት ሃያ ስድስት መስመር ነው፡፡ አምስትና ስድስት ዐሥራ አንድ ሃያና ዐሥራ አንድ ሠላሳ አንድ ሁለት መቶ ሠላሳ አንድ ። 
ቀመር ኃምስ ማቴዎስ ወሉቃስ ፹ወ፫ መስመር
ሁለቱ የተባበሩበት አምስተኛው ሰንጠረዥ ሰማንያ ሦስት መስመር ነው፤ ሠላሳና ሰማንያ መቶ ዐሥር፡፡ ሦስትና አንድ አራት ሦስት መቶ ዐሥራ አራት
ቀመር ሳድስ ማቴዎስ ወማርቆስ ፵ወ፰ መስመር
ሁለቱ የተባበሩበት ስድስተኛው ሰንጠረዥ አርባ ስምንት መስመር ነው ፤ ማርቆስና ሉቃስን አወጣ ሁሉንም እንዲህ እያልህ ሂድ ፤ ዐሥርና አርባ አምሳ አራትና ስምንት ዐሥራ ሁለት ። ሦስት መቶ ስሳ ሁለት ።
ቀመር ሳብዕ ማቴዎስ ወዮሐንስ ፯ መስመር
ሁለቱ የተባበሩበት ሰባተኛው ሰንጠረዥ ሰባት መስመር ነው፤ ሁለቱን ከሰባት ላይ ስትደርበው ዘጠኝ ይሆናል ሦስት መቶ ስሳ ዘጠኝ ማቴዎስ እስከ ሰባት ይዘምታል ከዚህ በታች የለውም ፤
ቀመር ሳምን ማርቆስ ወሉቃሰ ፲ ወ፫ መስመር ፤
ሁለቱ የተባበሩበት ስምንተኛው ሰንጠረዥ ዐሥራ ሦስት መስመር ነው ሦስት መቶ ሰማንያ ሁለት ይሆናል።
ቀመር ታስእ ሉቃስ ወዮሐንስ ፲ ወ፱ መስመር
ሁለቱ የተባበሩበት ዘጠነኛው ሰንጠረዥ ዐሥራ ዘጠኝ መስመር ነው ፤ ሁለትን ካሥራ ዘጠኝ ላይ ቢደርቡት ሃያ አንድ ይሆናል ሃያውን ከሰማንያ ላይ ቢደርቡት መቶ ይሆናል ፤ አራት መቶ አንድ፡፡
ቀመር ዐሥር በዘተሌለዩ ቦቱ ኩሉ ለለአሐዱ አሐዱ እምሰባክያን ፪፻ ፶ ወ፬ መስመር። ከአራቱ ወንጌላውያን አንዱም አንዱ እያንዳንዱ የተባበሩበት ዐሥረኛው ሰንጠረዥ ሁለት መቶ አምሳ አራት መስመር ነው። ማቴዎስ ፷ወ፪ መስመር ማቴዎስ ሰሳ ሁለት መስመር ነው፤ ማርቆስ ፳ወ፩ መስመር ማርቆስ ሃያ አንድ መስመር ነው ስሳና ሀያ ሰማንያ አንድና ሁለት ሦስት ሰማንያ ሦስት ፤ ሉቃስ ፸ወ፪ መስመር ፤ ሉቃስ ሰባ ሁለት መስመር ነው ፤ ሰባና ሰማንያ  መቶ አምሳ ፤ ሦስትና ሁለት አምስት ፤ መቶ አምሳ አምስት ፤ ዮሐንስ ፺ወ፱ መስመር  ዮሐንስ ዘጠና ዘጠኝ መስመር ነው በዘጠኝ ላይ አምስትን የደረቡ እንደሆነ ዐሥራ አራት ይሆናል ። ዐሥራ አራት እና ዘጠና መቶ አራት ሁለት መቶ አምሳ አራት ሆነ ፤ አራቱ የተባበሩበት አራት መቶ አንድ፡፡ የተለያዩበት ሁለት መቶ አምሳ አራት መላው ስድስት መቶ አምሳ አምስት፡፡
ወንጌል ቅዱስ ዘዜነወ ማቴዎስ ቃሉ ፳፻ ወ ፯፻
ማቴዎስ ያስተማረው የወንጌል ዘሩ ሁለት ሺህ ከሰባት መቶ ነው ።
ወንጌል ቅዱስ ዘዜነወ ማርቆሰ ቃሉ ፲፻ ወ ፯፻፤
ማርቆስ ያስተማረው የወንጌል ዘሩ ሺህ ከሰባት መቶ ነው ፤ አራት ሺህ ከአራት መቶ ይሆናል ።
ወንጌል ቅዱስ ዘዜነወ ሉቃስ ቃሉ ፳፻ ወ ፰፻
ሉቃስ ያስተማረው የወንጌል ዘሩ ሁለት ሺህ ከስምንት መቶ ነው ፤ ስምንት መቶና አራት መቶ ሺህ ከሁለት መቶ ይሆናል  ሰባት ሺህ ከሁለት መቶ፡፡
ወንጌል ቅዱስ ዘሰበከ ዮሐንስ ቃሉ ፳፻ ወ፯፻
ዮሐንስ ያስተማረው የወንጌል ዘሩ ሁለት ሽህ ከሰባት መቶ ነው ፤ ሰባት መቶና ሁለት መቶ ዘጠኝ መቶ ይሆናል ።
ወኮነ ድሙረ ቃሎሙ ለዓርባዕቱ ወንጌላት ፺፻ ወ፱፻
የአራቱ ወንጌላት የዘራቸው ቁጥር ድሙሩ ዘጠኝ ሽህ ከዘጠኝ መቶ ነው ።
ከመ ታእምሩ ኁልቈ ቃላቲሆሙ ለአርባዕቱ ወንጌላት ጸሐፍነ ለክሙ በጻጋሁ ለእግዚአብሔር
የአራቱ ወንጌላውያን የዘራቸውን ቁጥር ታውቁ ዘንድ እግዚአብሔር ገልጾልን ጻፍንላችሁ።
ወምኅባረ ቃሎሙሰ ለ፬ቱ ወንጌላት ፺፻ ፬፻ ወ ፵፱ አራቱ ወንጌላውያን በዘር የተባበሩበት ግን ዘጠኝ ሽህ ከአራት መቶ ዓርባ ዘጠኝ ነው ፤ የተለያዩበት አራት መቶ አምሳ አንድ ነው ። 
ወከመዝ ኃብሩ አርባዕቲሆሙ ፤
አራቱ ወንጌላውን በዚህን ያህል ዘር ተባበሩ ።
ዘብእሲ ማቴዎስ፤    
በገጸ ብእሲ የተመሰለ ማቴዎስ ፤ 
ዘአንበሳ ማርቆስ ፤
በገጸ አንበሣ የተመሰለ ማርቆስ
ዘላህም ሉቃስ ፤ 
በገጸ ላህም የተመሰለ ሉቃስ
ዘንስር ዮሐንስ ፤  በገጸ ንስር የተመሰለ ዮሐንስ፡፡
ዘልዑለ ይሠርር ወልዑለ ይጸርሕ ወልዑለ ይሰብክ ቃለ ወልደ እግዚአብሔር ለዓለመ ዓለም አሜን፡፡
አካል ከህልውና ተገልጾለት ንጽሐ ሥጋ ንጽሐ ነፍስ ንጽሐ ልቡና ተሰጥቶት ቀዳሚሁ ቃል ብሎ የተናገረ ዮሐንስ ።   
ስምንተኛ ጉባኤ
ይቆየን፡፡
**************
መልካሙ በየነ
ደብረ ማርቆስ፤ ኢትዮጵያ
08/06/2011 ዓ.ም

No comments:

Post a Comment