Friday, March 8, 2019

ወንጌል ቅዱስ ክፍል 29


 ====================
የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ወንጌል።
ቅዱስ ማቴዎስ እንደ ጻፈው ።
ምዕራፍ ፪።
                  ******
፳፪፡ ወሰሚኦ ከመ አርኬላዖስ ነግሠ ለይሁዳ ህየንተ አቡሁ ሄሮድስ ፈርሃ ሐዊረ ህየ።
                  ******
፳፪፡ በአባቱ በሄሮድስ ፈንታ ይሁዳን ለመግዛት አርኬላኦስ እንደ ነገሠ ሰምቶ ወደ ኢየሩሳሌም መሄድ ፈራ።
(ሐተታ) የክፉ ልጅ ክፉ እሱስ ያባቱን ክፋት ይተውናል ብሎ። አንድም ልጆቻቸው የሞቱባቸው የይሁዳ ሰዎች ልጆቻችን ያለቁ ባንተ ልጅ ምክንያት አይደለም ብለው ቢጣሉኝሳ ብሎ ደም ፈራ።
ወአስተርአዮ በሕልም በሕልም ነገረው።
ወተግኅሠ ውስተ ደወለ ገሊላ ገሊላ ገባ፤ ገኃሡ አጋእዝትየ እንዲል።
                  ******
፳፫፡ ወበጺሖ ኃደረ ውስተ ብሔር እንተ ስማ ናዝሬት።
                  ******
፳፫፡ ገሊላ ደርሶ ናዝሬት ገብቶ ናዝሬት በምትባል አገር ኖረ።
ከመ ይትፈጸም ዘተብህለ በነቢይ ከመ ናዝራዊ ይሰመይ ወልድየ።
ልጄ እንደ ናዝራዊ እንደ ሶምሶን ይባላል ተብሎ በነቢይ ቃል የተነገረው ይደርስ ይፈጸም ዘንድ ናዝሬት ገብቶ ኖረ።
(ሐተታ) እንዲህ የሚል ወዴት አለ? ቢሉ በፄዋዌ ጠፍቷል። በፄዋዌም እንደ ጠፋ በተግሣፀ ሰሎሞን ታውቋል። ይህስ እዝራ ነሥኦን ወአስተጋብኦን ይለዋል ብሎ ተናግሮት ሳይጻፍ የቀረ ነው። ተናግረውት የቀረውን ማምጣት ለሐዋርያት ልማድ ነው። ተዓቀቡ በመዋዕለ አፅራር ያለውን በከመ ይቤ ኢዮብ እንዳሉ እንደ ናዝራዊ እንደ ሶምሶን ይባላል ተብሎ በነቢይ የተነገረው ይደርስ ይፈጸም ዘንድ በናዝሬት ኖረ።
አንድም በኦሪቱ እስመ ናዝራዊ ሐዲስ ውእቱ ለእግዚአብሔር ያለውን እንዲህ ለውጦ አነበበው። ይህንማ የተናገረ መልአክ አይደለም ስለምን ነቢይ አለው ቢሉ፤ መልአክ ይሰመይ በእንተ ተልእኮቱ ወሐዋርያ ይሰመይ በእንተ ሐዊሮቱ እንዲል፣ ከዚያ በግብሩ መልአክ እንደ አለው ከዚህም በግብሩ ነቢይ አለው።
ያውስ ቢሆን ይህ የተነገረ ለሶምሶን አይደለምን ቢሉ። ለጊዜው ለሶምሶን ቢሆን ፍጻሜው ለጌታ ነውና። አነ እከውኖ አባሁ ወውእቱ ይከውነኒ ወልድየ ያለው ለጊዜው ለሰሎሞን ቢሆን ፍጻሜው ለጌታ እንደ ሆነ።
ያውስ ቢሆን በምን ይመስለዋልና እንዲህ አለ ቢሉ። ሶምሶን በተናቀች መንሰከ አድግ ጠላቶቹን እንዳጠፋ ጌታም አይሁድ አጋንንት መናፍቃን በናቁት ሞቱ ሞትን አጥፍቷልና። ሶምሶን በሕይወተ ሥጋ ሳለ ካጠፋቸው አሕዛብ በሞቱ ያጠፋቸው ይበዛሉ። ጌታም በሕይወተ ሥጋ ሳለ ካጠፋቸው አጋንንት በሞቱ ያጠፋቸው ይበዛሉና።
አንድም ከመ ናዝራዊ ይሰመይ ብለህ ናዝሬት ማለት ፍልጠት ክፍለት ማለት ነው። ልጄ ልዩ ይባል ዘንድ ናዝሬት ገብቶ ኖረ። ዘተብህለ በነቢይ ስሙ ለልዑል ቅዱሰ ቅዱሳን ወይትቀባዕ ቅዱሰ ቅዱሳን ያለው ይደርስ ይፈጸም ዘንድ።
አንድም ናዝሬት ማለት ኅሥርት ማለት ነውይእተ አሚረ ይሰምያ ለናዝሬት በስመ ኃሣር እንዲል። ልጄ ኅሡር ይባል ዘንድ ናዝሬት ገብቶ ኖረ እልህንሡር እንዲል በዓረብ ኅሡር ሲል።
አንድም ናዝሬት ማለት አጽቀ ጽጌ ማለት ነው። ልጄ አጽቅያዊ ጽጌያዊ ይባል ዘንድ ናዝሬት ገብቶ ኖረ። እሱ እንደ ጕንድ ምዕመናንን እንደ አዕፁቅ እንደ ጽጌያት አድርጎ ያስገኛልናያው ግን በነቢይ ቃል ትወጽእ በትር እምሥርወ ዕሤይ ወየዓርግ ጽጌ እምጕንዱ ተብሎ የተነገረው ደደርስ ደፈጸም ዘንድ ነው።
                  ******
በእንተ ስብከተ ዮሐንስ።
ምዕራፍ ፫ቱ።
                  ******
፩፡ ወበውእቱ መዋዕል በጽሐ ዮሐንስ መጥምቅ እንዘ ይሰብክ በገዳመ ይሁዳ ዘዮርዳኖስ።
፩፡ ከመ ናዝራዊ ይሰመይ ወልድየ ብሎ ነበርና ናዝራዊ በተባለበት ወራት ቦአ ናዝሬተ ብሎ ነበርና ናዝሬት በገባበት ወራት ሐያ አምስቱን ዘመን አንድ ወገን አድርጎ ወበውእቱ መዋዕል አለ በዮሐንስ አርባውን ቀን እንዳንድ ቀን አድርጎ ወአመ ሳኒታ እንዳለ።
                  ******
ይቆየን፡፡
**************
መልካሙ በየነ
ደብረ ማርቆስ፤ ኢትዮጵያ
29/06/2011 ዓ.ም

No comments:

Post a Comment