Sunday, March 24, 2019

ወንጌል ቅዱስ ክፍል 44


***ወንጌል ቅዱስ ክፍል 44***
 ====================
የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ወንጌል።
ቅዱስ ማቴዎስ እንደ ጻፈው።
ምዕራፍ ፭።
                  ******
፲፯፡ ኢይምሰልክሙ ዘመጻእኩ እሥዓሮሙ ለኦሪት ወለነቢያት።
                  ******
ብፁዓን ብፁዓን እያለ ሲያስተምር ሰምተው ኦሪትን ነቢያትን እንጂ ሊያሳልፋቸው መጥቷል እንዲሉት አውቆ አመጣ፡፡ እንዲሉትም አውቆ ማምጣት ልማድ ነው። ትውልደ አራዊተ ምድር ቢላቸው አብርሃምን ያህል አባት ሳለን ትውልደ አራዊተ ምድር ይለናል እንዲሉት አውቆ ኢይምሰልክሙ ዘታመስጡ በብሂለ አብ ብነ አብርሃም እንዳለ ወኢትሁቦ ለጻድቅከ ይርአይ ሙስና ቢላቸው ይህንማ ዳዊት ለራሱ የተናገረው አይደለም እንዲሉት አውቆ ታበውሑነሁ ኦ ሰብእ ንንግርክሙ ክሡት በእንተ ዳዊት ርእሰ አበው ከመሂ ሞተ ወተቀብረ ወኀቤነ ሀሎ መቃብሪሁ እስከ ዮም እንዳለ፤ ከዚህም እንዲህ አለ።
፲፯፡ ኦሪትን ነቢያትን ላሳልፋቸው የመጣሁ አይምሰላችሁ፡፡ ኢመጻኩ ይላል፡፡ ላሳልፋቸው አልመጣሁም።
ዘእንበለ ዳዕሙ ከመ እፈጽሞሙ፡፡
ፍጹማን ላደርጋቸው ነው እንጂ። ኢትቅትልን በኢታምፅዕ፤ ኢትፍቱን በዘርእያ ላጸናቸው ነው እንጂ። ወፈጸመ ሕገ ርትዕ በሕገ ትሩፋት አንዲል።
                  ******
፲፰፡ አማን አማን እብለክሙ እስከ አመ የሐልፍ ሰማይ ወምድር የውጣ እንተ አሐቲ ኅርመታ ወአሐቲ ቅርፀታ ኢተሐልፍ እምኦሪት ወእምነቢያት እስከ ሶበ ኵሉ ይትገበር ወይከውን፡፡ ሉቃ ፲፮፥፲፯።
                  ******
፲፰፡ ሰማይ ምድር እስኪያልፍ ይህ ሁሉ እስኪሆን ይህ ሁሉ እስኪደረግ ድረስ ሥርዓቷ ጽሕፈቷ አንዲት የምትሆን ኢትፍቱስ እንኳ ከኦሪት ከነቢያት ተለይታ አታልፍም ብዬ እንዳታልፍ በእውነት እነግራችኋለሁ፡፡ ዮድ ለአሌፍ አሥረኛ እንደሆነ ኢትፍቱም ለኢታምልክ አሥረኛ ናትና።
አንድም አሰራረዟ አቀራረጹዋ አንድ የምትሆን ዐሥርቱ ቃላት ሁሉ ሲያልፍ ከኦሪት ከነቢያት ተለይታ እንዳታልፍ አታልፍም ብዬ በእውነት እነግራችኋለሁ፡፡ በሀገራቸው ፲ቱ ሲሉ የውጣ ይላሉ አንዲት ጭራ ናት እዝል ቅጽል የላትም። በእኛም ፲ አንዲት ጭራ ናት ዕዝል ቅጥል የላትም፡፡
አንድም ለእኛ ፊደል ዐሥረኛው ተ ነው። መስቀላዊት ሕገ ክርስቶስ ወንጌል ከኦሪት ከነቢያት ተለይታ ወደሰው ልቡና አትገባም ብዬ እነግራችኋለሁ። ወኀለፈት ሰንበት እንዲል። አብራ ትነገራለች እንጂ ማለት ነው። ውኅጣ የሚል አብነት ይገኛል። የውጣ ማለት ነው ። በዳር ሮ ሎ ብሎ ይገኛል፤ ሮ ቢል ከመንግሥተ ሮም የምትበልጥ ሎ ቢል ልዕልት የምትሆን ወንጌል ከኦሪት ከነቢያት ተለይታ ወደሰው ልቡና አትገባም ብዬ እንዳትገባ በእውነት እነግራችኋለሁ።
                  ******
፲፱፡ ዘኬ ፈትሐ አሐተ እምእላ ትእዛዛት እንተ ተሐፅፅ ወይሜሕር ከመዝ ለሰብእ ሕፁፀ ይከውን በመንግሥተ ሰማያት። ያዕ ፪፥፲፡፡
                  ******
፲፱፡ ከዐሠርቱ ቃላት አንዲቱ ታናሻ ናት ብሎ ለራሱ የሚሠራ ለሌላው የሚያስተምር ውፁአ ሲል ነው፡፡ ከመንግሥተ ሰማያት የወጣ ይሆናል፡፡ መኑ አብ ኦ ለዘ እግዚአብሔር አሕፀፆ ወሐፀ መንፈቅ ወየሐፅፆሙ እመንግሥተ አቡሁ አንዲል።
ወዘሰ ይገብር ወይሜሕር ከመዝ ለሰብእ ውእቱ ዐቢየ ይከውን በመንግሥተ ሰማያት፡፡
ከዐሠርቱ ቃላት አንዲቱ ደግ ናት ብሎ ለራሱ የሚሠራ ለሌላው የሚያስተምር ግን ለመንግሥተ ሰማያት ባለቤት ይሆናል።
አንድም ይከውን ሕፁፀ፡፡
እንደ ጨረቃ እንደ ንዑስ ከከብ ይሆናል፣ ይከውን ዐቢየ እንደ ፀሐይ እንደ ዐቢይ ኮከብ ይሆናል።
                  ******
፳፡ ናሁ እብለክሙ ከመ ለእመ ኢፈድፈደ ጽድቅክሙ እምጸሐፍት ወፈሪሳውያን ኢትበውዑ ውስተ መንግሥተ ሰማያት። ሉቃ ፲፩፥፴፱፡፡
                  ******
፳፡ በቁሙ ጸሐፍት ፈሪሳውያን ናቸው ብሎ። ሥራችሁ ከጸሐፍት ከፈሪሳውያን ሥራ ከአልበለጠ ኢያፈድፈድክሙ ጸዲቀ አብዝታትሁ ሥራ ከአልሠራችሁ መንግሥተ ሰማያት አትገቡም ብዬ አንዳትገቡ በእውነትእነግራችኋለሁ። እኒያም አልገቡ እናንተም አትገቡ ማለት ነው።
አንድም ደጋጎች እለ አብርሃም እለ ሙሴ እለ ዳዊት ናቸው ብሎ ሊቁ ወስዶታል፡፡ ብሎ በሥራ መበላለጥ ከሌለ በክብርም መበላለጥ የለም ብዬ በእውነት እነግራችኋለሁ። ሥራው ምንደነው ቢሉ አፍቅሮ ጸላዕት፤ ተፀፍዖ መልታሕት፤ መንኖ ጥሪት ነው። ይህንማ እነሱስ አድርገውት የለም ለእመ ርኢከ አድገ ፀላዒከ ዘኃየሎ ፆሩ ኢትትዓደዎ አላ አስተልዕል ምስሌሁ እንዲል። ዘፀ
፳፫፥፭፡፡ አድርገውት የለም ቢሉ መጥዎተ ርእስ ነው፡፡ ይህንስ አድርገውት የለም ሙሴ እምትጥስዮሙ ለእሉ ሕዝብከ ጠስየኒ እመጽሐፈ ሕይወትከ ሏል። ዘፀ ፴፪፥፲፩፡፡ ዳዊትስ ምንተ ገብሩ እሉ አባግዕ እንዘ ኖላዊሆሙ አነ ዘአበስኩ። ዳዕሙ ለት እዴከ ላዕሌየ ወላዕለ ቤተ አቡየ ብሎ የለም ቢሉ፡፡ እኒያ ለዘመዶቻቸው ነው፡፡ እናንተ ግን ለሁሉ አድርጉት ሲል፡፡ እኒያ አስበውት ቀርቷል እናንተ ግን አድርጉት ሲል ነው፡፡
ዳግመኛ ሕግ ሁኖ ስላልተጻፈ ተጽፎ የለም ቢሉ ገብሩ ተብሎ ተጽፋል እንጂ ግበሩ ተብሎ ተጽፏልን። በሥራም ከአልተበላለጣችሁ ማለቱስ እንደ ምነው ቢሉ ለእኒያ አብነት አልነበራቸውም። ለኒህ ግን አብነት ጌታ አላቸወና፡፡ እኒያ በልጅነት አልታደሱም እኒህ ግን በልጅነት ታድሰዋልና።
ለኒያ አጋዥ አልነበራቸውም ለኒህ ግን አጋዥ ሥላሴ መላእክት መጸሕፍት መምራንአሏቸውና።
                  ******
፳፩፡ ሰማዕክሙ ዘተብሀለ ለቀደምትክሙ ኢትቅትል ነፍሰ።
፳፩፡ ለቀደሙ ሰዎች ነፍስ አትግደል የተባለውን፡፡ ዘፀ ፳፥፲፫፡፡
                  ******
ይቆየን፡፡
**************
መልካሙ በየነ
ደብረ ማርቆስ፤ ኢትዮጵያ
16/07/2011 ዓ.ም

No comments:

Post a Comment