Wednesday, March 13, 2019

ወንጌል ቅዱስ ክፍል 34


 ====================
የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ወንጌል።
ቅዱስ ማቴዎስ እንደ ጻፈው።
ምዕራፍ ፫።     
                  ******
፲፯፡ ወተጠሚቆ እግዚእ ኢየሱስ ሶቤሃ ወፅአ እማይ። ሉቃ ፫፥፳፩-፳፪፡፡
                  ******
፲፯፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተጠመቀ በኋላ ከውሃው ወጣ፡፡
(ሐተታ) ጥምቀቱን በውሀ ያደረገው በሌላ ያላደረገው ስለምን ቢሉ ትንቢቱ ምሳሌው ሊፈጸምትንቢት ወእነዝኃክሙ በማይ ንጹሕ ወትነጽሑ እምርኵስክሙ ተብሎ ተነግሯል።
ምሳሌም ለታውፅእ ባሕር ኵሎ ዘይትሐወስ ዘቦ መንፈሰ ሕይወት ባለ ጊዜ በልብ የሚሳቡ በእግር የሚያሽከረክሩ በክንፍ የሚበሩ በደመ ነፍስ ሕያዋን ሁነው የሚኖሩ ፍጥረታት ተገኝተዋል። በረው በረው የሄዱ አሉ ከዚያውም የቀሩ አሉ። በረው የሄዱ የኢጥሙቃን ከዚያው የቀሩ የጥሙቃን ምሳሌ። ይህስ እንዳይሆን ወባረኮሙ ለክልኤሆሙ በአሐቲ በረከት ይላል ብሎ በልብ የሚሳቡ የሰብአ ዓለም በእግር የሚያሽከረክሩ ከትሩፋት ወደ ትሩፋት የሚሉ የባሕታውያን። በክንፍ የሚበሩ ተመስጦ ያላቸው የሰማዕታት ምሳሌ።
ትንቢቱን አውቆ አናግሯል ምሳሌውንም እንጂ ባወቀ አስመስሏል። ፍጻሜው እንደምነው ቢሉ ውሀ በዙፋን ከለ ንጉሥ ባደባባይ እስካለ ጽኑስ ለሁሉ ርኩብ ነው ጥምቀት መሠራቱ ለሁሉ ነውና።
ውሀ ጽንፍ እስከ ጽንፍ ይፈሳል። ጥምቀትም ጽንፍ እስከ ጽንፍ ይደረጋልና።
ውሀ ያነጻል ጥምቀትም ያነጻልና።
ውሀ ለወሰደው ፍለጋ የለውም። በጥምቀትም የተሰረየ ኃጢአት በፍዳ አይመረመርምና።
ውሀ መልክ ያሳያል መልክ ያለመልማል። ጥምቀትም መልክአ ነፍስ ያሳያልና መልክአ ነፍስን ያለመልማልና። በውሀ የታጠበ ልብስ ኃይል ጽንዕ ግዘፍ እየነሣ ይሄዳል ምዕመንናም ተጠምቀው ገድል ትሩፋት እያከሉ ይሄዳሉና።
አንድም ሥጋዊ ተፍኅሮ የነርብቃ የነሲፓራ በውሀ ምክንያት ሁኑዋል መንፈሳዊ ተፍኅሮንም በውሀ ለማድረግ።
አንድም ሸክላ ሠሪ ሠርታ ስትጨርስ የነቃባት እንደሆነ እንደገና ከስክሳ በውሀ ለውሳ ታድሰዋለች። ተሐድሶም በጥምቀት ነውና።
አንድም በውሃ ቀድሞ ሰብአ ትካትን ኋላ ግብፃውያንን ከጠፋበት በኋላ ለመዓት እንጂ ለምሕረት አልተፈጠረም ብለውታል። ለምሕረትም አንደተፈጠረ ለማጠየቅ።
(ሐተታ) የወዲያኛው ቀስቱን እያጋለ መርዝ እየቀባ እያተባ ይመጣል። የወዲህኛውም እግዚአብሔር ጥበቡን ገልጾለት ጀርባውን ከውሀ ነክሮ ለጋሻው አልብሶ ይሄዳል መርዙን ጀርባው ይጠርግለታል ግለቱን ውሀው ያቀዘቅዝለታል ስለቱን ጋሻው ይመልስለታል እንደዚህ ሁሉ ምዕመናንም በጥምቀት ባገኙት ኃይል ድል ይነሳሉና።
ወናሁ ተርኅወ ሎቱ ሰማይ።
ሰማይ ተከፈተለት
(ሐተታ) በሰማይ መከፈት መዘጋት የለበትም ደጅ በተከፈተ ጊዜ የውስጡ እንዲታይ ያልተገለጸ ምሥጢር ተገለጸለት ሲል ነው።
ወርአየ መንፈሰ እግዚአብሔር እንዘ ይወርድ ከመ ርግብ ወነበረ ላዕሌሁ። መንፈስ ቅዱስ በአምሳለ ርግብ ወርዶ በራሱ ላይ ሲቀመጥበት አየ።
(ሐተታ) መንፈስ ቅዱስን ርግብ አለው ርግብ ኃዳጊተ በቀል ናት። መንፈስ ቅዱስም ኃዳጌ በቀል ነውና።
አንድም ርግብ በኖኅ ጊዜ ሐፀ ማየ አይኅ ነትገ ማየ አይኅ ስትል ቈፅለ ዕፀ ዘይት ይዛ ተገኝታለች፤ መንፈስ ቅዱስም ተስፋ መስቀልን ያበስራልና።
አንድም ርግብ ክንፏን ቢመቷት ዕንቊላሏን ቢሰብሩባት ቤቷን ካላፈረሱባት አትሄድም። መንፈስ ቅዱስም ኃጢአት ቢሠሩ ፈጽመው ካልካዱት አይለይምና። (ታሪክ) አንድ ባሕታዊ እንዳየው ወለተህነ ግልፎን አጊጣ አይቶ በሐፀ ዝሙት ተነደፈ። ላግባሽ አላት ላባቴ ንገረው እምቢ አይልህም አለችው ሂዶ ነገረው።
ፈጣሪዬን ልጠይቅ ብሎ ከጣዖቱ ዘንድ ገብቶ ልስጠው አልስጠው ብሎ ጠየቀው። ቆቡን ይቅደድ ፈጣሪውን ይካድ ይኸን ካላደረገ አትስጠው አለው ሂዶ ነገረው። ቆቡን ቀደደ ፈጣሪውን ካደ። በዚህ ጊዜ አድሮበት የነበረ መንፈስ ቅዱስ በነጭ ርግብ አምሳል ለይቶት ሲሄድ አይቷል። ያልኸኝን አደረግሁ ስጠኝ አለው ሁለተኛ ልጠይቅ ብሎ ገብቶ ቢጠይቀው። ቈይ ፈጣሪውም ፈጽሞ አልራቀውም ባጠገብ ባጠገቡ ይጠብቀዋልና አትስጠው አለው። አይሆንም አለው ለዚህን ብዬ ፈጣሪዬን ካድሁ ቆቤን ቀደድሁ ብሎ ንስሐ ቢገባ መልሶ በርግብ አምሳል ሲያድርበት አይቷል።
ጥምቀቱን በመዓልት ያላደረገው በሌሊት ያደረገው ስለምን ቢሉ። በመዓልት አድርጎት ቢሆን መንፈስ ቅዱስን በቁሙ ርግብ ነው ብለው በተጠራጠሩ ነበርና። አሁንስ በቁሙ ርግብ አለመሆኑ መንፈስ ቅዱስ መሆኑ በምን ይታወቃል ቢሉ። ጌታ የተጠመቀ ከሌሊቱ ባሥረኛው ሰዓት ነው በዚያን ጊዜ ተሐዋስያን ከየቦታቸው አይናወጡምና። በቁሙ ርግብ አለመሆኑ መንፈስ ቅዱስ መሆኑ በዚህ ይታወቃል።
መንፈስ ቅዱስም መውረዱ ከውሀው ከወጣ ከዮሐንስ ከተለየ ነው። ከውሀው ሳለ ወርዶ ቢሆን ለቀድሶተ ማያት የወረደ ነው ባሉ ነበረና ከዮሐንስ ጋራም ሳለ ቢሆን ስለ ክብረ ዮሐንስ የወረደ ነው ባሉ ነበርና።
ረቦ ወርዷል ያሉ እንደሆነ አብ ምሉዕ ነው አንተም ምሉዕ ነህ እኔም ምሉዕ ነኝ ሲል።
አሰይፎ ወርዷል ያሉ እንደሆነ የብሉየ መዋዕል የአብ ሕይወት ነኝ የብሉየ መዋዕል ያንተም ሕይወት ነኝ እኔም ብሉየ መዋዕል ሕይወት ነኝ ሲል።
ወርዶ ራሱን ቆንጠጥ ኦድርጎ ይዞታል አብ አኃዜ ዓለም ነው አንተም አኃዜ ዓለም ነህ እኔም አኃዜ ዓለም ነኝ ሲል። መውረዱ ግን የማኅፀኑን ለመግለጽ ነው። አንድም ለአብነት እናንተም ብትጠመቁ እንዲህ ይወርድላችኋል ለማለት።
                  ******
፲፯፡ ወናሁ መጽአ ቃል እምሰማይ ዘይብል ዝንቱ ውእቱ ወልድየ ዘአፈቅር ዘቦቱ ሠመርኩ። ሉቃ ፱፥፴፮። ፪፡ጴጥ ፩፥፲፮።
                  ******
፲፯፡ ለተዋሀዶ የመረጥሁት በሱ ህልው ሁኜ ልመለክበት የወደድሁት ልጄ ይህ ነው የሚል ቃል ከወደ ሰማይ ተሰማ።
(ሐተታ) በዚህ አድሮ ያለው ልጄ ነው አላለም። አንድ አካል አንድ ባሕርይ አድርጎ ይህ ልጄ ነው አለ እንጂ። ኢይቤ ዘላዕለ ዝንቱ ወልድየ አላ ይቤ ዝንቱ ውእቱ ወልድየ እንዲል። ወልድየም ማለቱ እንደ አምላክነቱ ነው እንጂ እንደ ሰውነቱ አይደለም። ኢይቤ ዝንቱ ወልድየ ዘከመ ትስብእቱ አላ ይቤ ዝንቱ ውእቱ ወልድየ ዘከመ መለኮቱ እንዲል።
                  ******
በእንተ ተመክሮት ዘኢየሱስ።
ምዕራፍ ፬።
፩፡ ወእምዝ ወሰዶ መንፈስ ገዳመ ለእግዚእ ኢየሱስ። ማር ፩፥፲፪። ሉቃ ፬፥፭።
፩፡ ከተጠመቀ በኋላ ፈቃዱ አነሣስቶ ወደ ገዳም ወሰደው።
                  ******
ይቆየን፡፡
**************
መልካሙ በየነ
ደብረ ማርቆስ፤ ኢትዮጵያ
04/07/2011 ዓ.ም

No comments:

Post a Comment